አሥር ከፍተኛ የደርግ ባለሥልጣናት ይፈታሉ

9 Jun

በዘር ማጥፋት ወንጀል ከተከሰሱት 23 ከፍተኛ የደርግ ባለሥልጣናት መካከል 20 ዓመት የታሠሩት አሥር ከፍተኛ የደርግ ባለሥልጣናት ይፈታሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ባለፈው ሳምንት 23ቱ ባለሥልጣናት የተፈረደባቸው የሞት ፍርድ በፕሬዚዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ወደ ዕድሜ ልክ ዝቅ መደረጉን ተከትሎ፣ ታስረው 20 ዓመት የሞላቸው ባለሥልጣናት እንደሚለቀቁ ታውቋል፡፡

ቀሪዎቹም ባለሥልጣናት 20 ዓመት እንደሞላቸው ጊዜያቸውን ጠብቀው ይለቀቃሉ፡፡ ከ23ቱ መካከል በደርግ ዘመን የደኅንነት ሚኒስትር የነበሩት ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደ ሥላሴ ግንቦት 27 ቀን 2003 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ መሆኑ ይታወሳል፡፡

አሥሩ ባለሥልጣናት ከማረሚያ ቤቱ ሰባት ገጽ ያለው ቅጽ ወስደው እንደሞሉ ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ማረሚያ ቤቶች ምክትል ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ወልዳረጋይ ለዋልታ እንደገለጹት፣ ባለሥልጣናቱ በማረሚያ ቤት ቆይታቸው ብዙ ተምረዋል፡፡ ባለሥልጣናቱ ከኅብረተሰቡ ጋር አብሮ የመኖር ችግር እንደማይገጥማቸው አክለው ገልጸዋል፡፡

አሁን በእስር ላይ የሚገኙት ባለሥልጣናት ሻምበል ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ፣ ሻምበል ለገሰ አስፋው፣ ሻለቃ መላኩ ተፈራ፣ አቶ አብዱልቃድር መሐመድ፣ ጄኔራል ለገሠ በላይነህ፣ አቶ ገስግስ ገብረ መስቀል፣ መቶ አለቃ ጴጥሮስ ገብሬ፣ መቶ አለቃ ስለሺ መንገሻ፣ ኮሎኔል ናደው ዘካሪያስ፣ ሻምበል በጋሻው አታላይ፣ ሜጀር ጄኔራል ውብሸት ደሴ፣ ኮሎኔል ፍስሐ ደስታ፣ ኮሎኔል እንዳለ ተሰማ፣ ኮሎኔል ደበላ ዲንሳ፣ መቶ አለቃ አርጋው ይመር፣ ሻለቃ ደጀኔ ወንድማገኘሁ፣ አቶ እሸቱ ሸንቁጤ፣ ሻምበል ገሠሠ ወልደ ኪዳን፣ መቶ አለቃ ደሳለኝ በላይ፣ ወታደር ልሳኑ ሞላ፣ ወታደር አበበ እሸቱና ወታደር ዘሪሁን ማሞ ናቸው፡፡

Ethiopian Reporter

Leave a comment